Monday, July 30, 2012

ጥቁሯ ቦርሳዬ
ክፍል 9
በግሩም ተ/ሀይማት

ሰላም ናችሁልኝ? ስላም ያድርጋቸሁ፡፡ የምመኝላችሁ ሰላም ነው፡፡ የዚህ ክፍል መልዕክት ‹‹አራዳ ለመሆን ከመፈንዳት ሰርቶ ይዞ መገኘት..›› የሚል ነው፡፡ አንኳር መልዕክቱን ወደታች ስንወርድ ፈረካክሰን እናያለን፡፡

አንድ በሉልን ፍቅር ልብስ የሚያስወልቀን አንሶ ሙቀትም ልብሳችንን እያስወለቀን ነው-የመን፡፡ ለስንቱ አውልቀን እንችላለን? ለፍቅር የምናወልቀው አንሶ ስል አሳብዶን እንዳይመስላችሁ..ያው ህብረ-አንሶላ ለመፍጠር..አይ እናንተ አሳፈራችሁኝ፡፡ ታዲያ በዚህን ሙቀት ቁም ነገር ብቻ ማውራት ሲያልብ በብርጭቆ ወረቀት እንደመጥረግ ይቆጠራል፡፡ ለነገሩ ብዙ ሲሪየስ ወግ አወጋኋችሁ፡፡ ድክም ያላችሁ ባይመስልም አረፍ እንድትሉ ፈለኩ፡፡ ምን መፈለግ ብቻ ከተመቻችሁ እና ጥርሳችሁ ከመጣ መሳቅ ይችላል፡፡ ታዲያ አደራ ሲትስቁ ንገሩን እኛም እናጅቦት፡፡ ምናለበት ዘንድሮ ሁሉን ነገር ቀየር አድርገን ባልተለመደ ሁኔታ ብንጓዝ? ብቻ ከማግጠጥ በአጃቢ መሳቅ ደስ ይላል፡፡ ከተቻለ አጀባውን በባንድ እናደርገዋለን፡፡ እንዳልኳችሁ ዘንድሮ ባልተለመደ መንገድ ብንጓዝ ምን ይመስላችኋል? ሀበሻ ምቀኛ ነው የሚለውን ለውጠን ሀበሻ የሚተጋገዝ፣ የሚረዳዳ ነው ለመባል እንጣር፡፡ ሀበሻ ምቀኛ ነው፣ ወሬኛ ነው፣ ተንኮለኛ ነው...እያለ የሚያወራው ራሱ ሀበሻ መሆኑ ደግሞ ይበልጥ የሚያስገርመኝ ነው፡፡ እንዴት ሰው ራሱን ይሰድባል? ደሙን አላስወጣ፣ አላስለወጠ አፉን ሞጥሞጥ አድርጎ ብቻ ሀበሻ ሲባል…ይላል፡፡ ራሱን መስደብ ራሱን ማዋረድ የለመደ ህሊና እንዴት ራሱን ከፍ ማድረግ ያስብ..ባልተለመደ መንገድ እንጓዝ ያልኳችሁም ለዚህ ነው ይሄን ሰንካላ አባባል ጥለን እብስ….

ታዲያ ይህን ጥለን ስንጓዝ የአራዳ ልጅ ነን እያልን በባዶ መኮፈስንም አስቀምጠናት እንለፍ፡፡ ተግቶ በማስራት ስለሆነ መለወጥ የላጪን ልጅ ቅማል በላው እንደሚባለው ያራዳን ልጅ ፋራ በላው እንበል? ጎበዝ እንዳትጃጃሉ ግጥም አድረጎ በልቶታል፡፡ ፋራ የተባለው አቀርቅሮ ሲስራ አራዳ የተባለው ሙድ ሲይዝ ሙዱ ጉዱ ሆኖት ቀርቷል፡፡ አራዳ ማለት በልጦ መገኘት ነው፡፡ አራዳ ማለት ሰርቶ ማግኘት ይሁን እስኪ..አራዳ ማለት ይዞ መገኘት ነው፡፡ አራድነታችሁን ካልተጠቀማችሁበት እንደ እኔ ኑሩበት፡፡ እኔን ብታዩ በኑሮዬ አራዳ ነኝ፡፡ ያውም ሴንተሩ ላይ…ቤቴን ነው ያልኳችሁ፡፡ ማለቴ አራዳ ክ/ከተማ ነኝ፡፡ አሁን አራዳ ለክፍለ ከተማነት መጠሪያ ብቻ ቢያገለግል ነው የሚመረጠው፡፡ ልብስ ማንኳተት ቃላት ማንጋተት ጥቅም የለውም፡፡

አቤት ይሄን የሚያነቡ የአራዳ ልጅ ተብዬዎች…ልመቻችሁ ብሎ…ማለታችው አይቀርም….በቃ አኩርፈውኝ አጠገባቸው ሆኖ ላጤናቸው ፊታቸው ለጉድ ተዘፍዝፎ ይታያል፡፡ ይህቺ ፊትህን ዘፈዘፍከው፣ ጣልከው የአንድ ሰሞን ቋንቋ ነበረች፡፡ የአራዳ ልጆች የተሻሻለች ስድብ ናት፡፡ አሁንም ትሰራለች፡፡ በቃ! እነዚህ እነ እንትና አራዳ ነን ብለው ሞራላችን ላይ እቃ..እቃ ተጫወቱብንኮ የምሬን ነው፡፡ እርድና ቋንቋ ማበላሸት ነው እንዴ? አንዱ አንድ ቀን ምን አለኝ መሰላችሁ? ምነው ጣልከው አለኝ፡፡ ዞር ብዬ የጣልኩት ነገር እንዳለ ስፈልግ ሳቀ፡፡ እምቢኝ ብሎ ከከንፈሩ አምልጦ ውጪ ያደረ ጥርሱን የበለጠ አስገጥጦ ተንከተከተ፡፡ እንሹካ የተገተረ ጥረሱን ለመሰብሰብ እየሞከረ ‹‹ፊትህን ጣልከው ነው ያልኩህ..›› አለኝ እና አረፈው፡፡

በእውነት ፋራ አይደለሁ ጣልከው ሲለኝ ላነሳ መዞሬ? አሁን በእናታችሁ የእኔ ፊት ጣልከው የሚባል ነው? መደመሪያውኑ የሰላሌን ሜዳ መስሎ ወድቆ የለ? የፊቴን ስፋት ልብ አላለውም እንጂ ከመስፋቱ የተነሳ ግማሹን አሳርሼ ግማሹ ላይ የሪል ስቴት ግንባታ መጀመሬን ቢያውቅ ጣልከው ባላለ፡፡ ውይ የእኔ ነገር ፊቴ የሚታያችሁ መስሎኝ ነው እኮ፡፡ እውነትም ፋራ ነኝ አይደል? እኔ የምለው ከምር እንነጋገር እስኪ ፀጉር ካላሳደኩ፣ የተንጀላጀለ ሱሪ ካለበስኩ፣ መርገጫው ሸክም የሆነ መጫሚያ ካልተጫማሁ፣ ቋንቋ ካላንሸዋረርኩ አራዳ አልባልም ማለት ነው?

አንድ ሰሞን ብቅ የሚሉ አባባሎችን እንመልከት እስኪ..ይመችህ ይመችሽ፣ አይ-ደል? የራስሽ..የራስህ ጉዳይ፣ ንገረው ለእገሌ ንገሪው ለእገሌ፣ ሲላጥ ሲላላጥ../ሰው እንደ ድንች እንደ ሽንኩርት ሲላጥ ይታያችሁ../ ደሞ እነሱ እንደሚያደርጉት ቃላትን ያለቦታቸው ሸጉጠን የአነጋገር ፋሽን ካልተከተልን አራዳ አይደለንም ማለት ነው? እኔን የፈለገ ፋራ ይበለኝ እንጂ አልጠቀምም፡፡ ከዚሁ አንድ ሰሞን ብቅ ከሚሉ ሰሞነኛ ቃላት ዙሪያ ሳልወጣ ‹‹ፍንዳታ›› ስለምትለው ቃል አስባችሁ ታውቃላችሁ? ፈነዳ፣ ፈነዳች..ፍንዳታ! ሆሆይ..በቃ! ፈነዳ የሚለው ቃል እኮ ትርጉም አጣ ማለት ነው፡፡ የተስፋዬ ካሳ ቀልድ ላይ ፈንዱ..የምትለውን የእንግሊዘኛ ቃል ታካ ‹‹..ካልፈነዳን አትረዱንም?..›› የምትል አባባል አለች፡፡ አስቃን አልፋለች፡፡ የአሁን ፍንዳታ ትርጉም ግን የተለየ ነው፡፡

እስኪ በእናታችሁ አንድ ነገር ላስቸግራችሁ፡፡ ብዙ አይደለም የማስቸግራችሁ አይናችሁን ጨፈን አድርጉ እና በምናባችሁ ሰው ሲፈነዳ ለማየት ሞክሩ፡፡ አያችሁ? ቆይ አረ እኛም ፈንድተን ነበር እንዴ? ወይ ጉድ ለካ ሳናውቀው ፈንድተን አልፈናል፡፡ ንገሩኝ እስኪ ፍንዳታ የሚለው ፊቱ ላይ ቡግር ወጥቶ የፈነዳለት ነው? ያኔ ነው ሀገሬ እያለሁ ፍንዳታ የሚባሉት ምን አይነቶች እንደሆኑ ለማወቅ ዳዳሁና አንድ የሰፈሬን ጎረምሳ /በእነሱ አጠራር ፍንዳታ ልበለው?/ ጠየኩት፡፡ የተለያዩ ምልክቶችን እና የሚያሳዩትን ባህሪ ነገረኝ፡፡ ለምሳሌ እንደ እገሊት ብዬ የሆነች ልጅ ጠቀስኩለት፡፡ ‹‹ውይ እሷማ ፈንድታ ጨርሳ ስትፈነዳ ያዝረከረከችውን አሁን እየሰበሰበች ነው..›› አለኝ፡፡ ድንቅ አነጋገር ነው፡፡ ሲፈነዱ ያዝረከረኩትን ሲያልፉ መሰብሰብ መቻሉም ጥሩ ነው፡፡ ግና እንዴት?

እዚህ ጋር ከአንድ ቴያትር ላይ የመዘዝኩትን አባባል ላዳምቅበት፡፡ ‹‹ከዘጠኝ ቀሚስ ለበስ ፈላስፋ ጋር ቁጭ ብሎ ከማውራት ኩንታል ድማሚት ላይ ተቀምጦ መፈንዳትን እመርጣለሁ…›› ከዳንዲዬ ጨቡዴ ቴያትር ላይ ነው የወሰድኩት፡፡ ከፈለገ እሱ ይፈንዳ እንጂ ፈንዱ ለማለት ሳይሆን መዝዤ ያወጣሁት መፈንዳት ድማሚት ላይ ተቀምጦ እንጂ እንዲሁ እንዴት ይፈነዳል? የሚለውን እንድታስቡት ነው፡፡ ጃክ ኤንድ ፋት ማን ፊልም ላይ የሚሰራው ፋትማን ፈንድቶ ነው የሞተው ሲባል ሰምቻለሁ፡፡ እሱስ ውፍረትም ነበረው የእኛን እኮ ዝም ነው፡፡ የምር ቋንጣም ይፈነዳል እንዴ? ነገሩ እንደዛ ነው የሆነብኝ፡፡

እዚህ የመን ግን ነገር ተገልብጧል፡፡ ፍንዳታውንም፣ ማፈንዳቱንም፣ መፈንዳቱንም በደንብ ያውቁታል፡፡ ትላንት እንኳን አንዱ የታጠቀውን አፈንድቶ እሱም ፈንድቶ አስር ሰዎችን አስከትሎ ነጎደ፡፡ አሸባሪዎቹ ይህን ፍንዳታ እና ማፈንዳት ይዘውታል፡፡ ፍንዳታ ማለት እንሱ ናቸው፡፡ የፈነዱ የሚፈነዱ….ሜይ 21 ቀን ወታደሮች ሰልፍ ልምምድ ላይ እያሉ ያፈነዳው 103 ወታሮችን በታትኗል፡፡ ስጋቸው እንደ አሸዋ ክምር በአካፋ እስኪዛቅ፡፡ ግሩም ፈነዳ ቢሏችሁ ጎረመሰ መስሏችሁ ዝም እንዳትሉ፡፡ አንድ ፎቅ የሚበታትን ፈንጂ የታጠቀ ከገጠመኝ ነው፡፡ አይግጠም ነው፡፡ እዚህ እውነተኛው ፍንዳታዎች ናቸው፡፡

ልጄ ለአቅመ ሔዋን ደረሰች፣ ልጄ ለአቅመ አዳም ደረሰ በማለት ፋንታ ልጄ ፈነዳ/ፈነዳች/ ልንል ነው? ስለ ፍንዳታዎች ባህሪ የምታውቁ እስኪ ጻፍ ጻፍ አድረጉና አስነብቡን፡፡ በአንድ ወቅት የቡሄ ሰሞን በየመንደሩ ርችት የሚያፈነዱ በዝተው ነበር፡፡ ሽማግሌው ኪስ፣ ጫማ..ውስጥ እየከተቱ ‹‹ጧ!..›› ያደርጋሉ፡፡ ያፈነዳሉ እንጂ አይፈነዱም፡፡ ሰው ያስደነግጣሉ፣ ጆሮ ያደነቁራሉ፡፡ ታዲያ ማን ይሙት እነዚህን ልጆች እደጉ ተመንደጉ አመት አመት ያድረሳችሁ ብሎ የሚመርቃቸው ይኖራል ብላችሁ ታስባላችሁ ? ወይድ በአጭር ያስቀርህ፣ ያፈንዳህ ከማለት የዘለለ ማን ሊቸራቸው? ያፈንዳህ እየተባሉ ይሆን ፍንዳታ የሆኑት? እንጃ ብቻ እንጃ፡፡ ‹‹ከመፈንዳት አካባቢን ማጽዳት›› የምትል ጽሁፍ አካባቢያቸውን ያሳመሩ ልጆች ጽፈው አይቻለሁ፡፡ አሪፍ አይደለች? አራዳነት በስራ የሚለውን አይጠቁምም ብላችሁ ነው? ድሮ ድሮ አራዳ ማለት ያለውን የሚያካፍል እንጂ ቁጭ ብሎ የሰው እጅ የሚጠብቅ አይደለም፡፡ እንደዛማ ከሆነ በልመና የተሰማሩ ሁሉ አራዳ ናቸው ማለት ነው፡፡ የሰው እጅ ከማየት ሰርቶ ማግኘት፡፡ አራዳነት ይዞ መገኘት፤ ሰርቶ መለወጥ ከሆነ ቆየ ያላወቃችሁ አራዶች ንቁ!!!!...
ሰላም ሁኑ!!..


ጥቁሯ ቦርሳዬ ክፍል 8
‹‹..ፍቅርን በአረቢኛ እንዴት ታነንሾካሹክለት ይሆን?.. ››
ወግ በግሩም ተ/ሀይማኖት

‹‹ሀሎ! ጤና ስጥልኝ!...›› አልኩ ሞባይል ስልኬን ከፍቼ፡፡ የደወለልኝን ሰው ቁጥር ከዚህ በፊት ባላውቀውም ተገቢው ሰላምታ ይድረሰው ብዬ ነበር ሰላምታ ማቅረቤ...

‹‹ምን ጤና ይሰጠኛል ጤና የነሳኝን ወሬ ላቀብልህ ነበር..›› ብስጭት የታከለበት ጎርናና ድምጽ ነው፡፡

‹‹ደስ ይለኛል ወዳጄ መቼ ላገኝህ እችላለሁ?›› ላልኩት ጥያቄ የሰጠኝ ምላሽ አሁኑኑ የሚል ሆኖ የት እንዳለሁ ጠየቀኝ፡፡ ነገርኩት፡፡ ሩቅ ቦታ ስለሆነ ከአንድ ሰዓት በኋላ እኔ ጋር እንደሚደርስ ነግሮኝ ተለያየን፡፡ እሱ እስኪመጣ ሰላምታዬን ለእናንተ ላድርስ፡፡ ሰላም ጤና ፍቅር ይስጣችሁ፡፡ የእዚህ ክፍል መርህ /መልዕክት/ ‹‹አስተውሎ መራመድ ብልህነት ነው..›› የሚል ነው፡፡ በእርግጥም አስተውለን የምናደርገው ነገር ፀፀት፣ ጉዳት፣ መጥፎ ስም፣ ህሊና የሚያስወቅስ ጭፍንነት.. የመሳሰሉትን ጉድፎችን አያስከትልም፡፡ አስተውሎ መራመድ ከግባችን መድረሻ አቋራጭ መንገድ ነው፡፡ ስለዚህ ምርጫችን ይሁን፡፡

ሀበሻ እና ቀጠሮ ፀባቸው የከረረ ይመስል እስካሁን አልታረቁም፡፡ በቀጠሮ ሰዓት መገኘት ክብር የሚቀንስ እየመሰለን ይሁን እንደ በሽታ ተጠናውቶን በማርፈድ ታውቀናል፡፡ ‹‹የሀበሻ ቀጠሮ..›› እያልን ተጠናውቶናል፡፡ ለነገሩ ‹‹ማርፈድ የስንፍና ምልክት ነው..›› እየተባለ የሚጻፍበት ግንብ እና በር ያለው ትምህርት ቤት ብንማርም ማርፈድ አርቆ የማሰብ ውጤት ነው የተባልን ይመስል በርትተን ተያይዘነዋል፡፡ አንዳንዱማ ለሁለት ሰዓት ቀጠሮ አራት ሰዓት ከቤቱ የሚነሳ አለ፡፡ ይህ ሰው ራሱን ይመርምር ዓለም ከሚጓዝበት ምህዳር በሁለት ሰዓት የዘገመ ሊሆን ይችላል፡፡ ጎበዝ ቀጠሮን እናክብር በሰዓት /በጊዜ/ ስንቀልድ በተገላቢጦሽ እየቀለደብን ነው፡፡

ከአንድ ሰዓት በኋላ ያለኝ ቀጣሪዬ ሶስት ሰዓት ከሀያ ደቂቃ ያህል ቆይቶ መጣ፡፡ ለምን አረፈድክ ብሎ መጠየቅም መቆጣትም አይቻልም፡፡ የሀበሻ ወጉ ማርፈድ ነውና ወግ ጠባቂ ብሎ ‹‹እንኳን ደህና መጣህ›› ብቻ ማለት ነው፡፡ ለነገሩ ያለሁት ሱቅ ውስጥ ስለሆነ ቢመጣም ባይመጣም እዛው ነኝ የት መሄጃ አለኝ? ቁጭ ብለን አወጋኝ፡፡ ስስቅ፣ ሳዝን፣ በስራችን ሳፍር አዳመጥኩት፡፡ የሰማነውን በልቦናችን ያሳድርልን…የሚለውን ቀየር አድርጌ የሰማሁትን በፌዝቡክ ላይ ያኑርልኝ ብዬ አሳረፍኩት እነሆ፡-

ፌዝቡክ ላይ የምትፅፋቸውን እከታተልሀለሁ፡፡ የመን ያሉ አስገራሚ እና አሳዛኝ ታሪኮችን ስታነሳ የእኔ ቢቀርብ ብዬ ነው አለኝ፡፡ ወደ ዋናው ወሬ ሲገባ ደግሞ ‹‹..ከሚስቴ ጋር የተዋወቅነው ቤት ልትከራይ መጥታ ነው፡፡..››ሲል ትረካውን ጀመረ፡፡ ያው ወሬው አደባባይ ሊውል ከተጀመረ ወደኋላ ምን ያደርጋል? ፍርጥርጥ እንዲያደርገው የሚል እሳቤ መጣብኝና ‹‹እንዴት?›› የሚል ጥያቄ አቀረብኩለት፡፡

ያው ታውቀዋለህ እዚህ ሀገር ሶስት ክፍል ቤት ነው የምትከራየው ከዛ የምትይዘውን ክፍል ትይዝና ቀሪውን ለሌላ ማከራየት ነው፡፡ ለደላላዎች ነግሬ ስለነበር ለኮንትራት ስራ መጥታ ሁለት አመት ሳትሰራ በሚደርስባት በደል ተማራ የጠፋች ልጅ በደላላው አድራሽነት እኔ ጋር ያለውን ቤት ልትክራይ መጣች፡፡ ተስማማን እና ኪራዩን ከፍላኝ እቃ ልግዛ ብላ ስትሄድ ሀገሩን ስለማታውቅ ላጋዛት ሄድኩ፡፡ ፍራሽ ብቻ ነው የገዛችው፡፡ ማደሪያ ስለ ሌላት ልታድርበት ነው ፍላጎቷ፡፡ አንሶላ የለ ብርድ ልብስ..አሳዘነችኝ፡፡ እዚህ ላይ እንዴት ትተኛለሽ እኔ ጋር ግቢ እና አልጋው ላይ ተኚ እኔ መሬት እተኛለሁ አልኳት፡፡ ተስማማን አደረች፡፡ በማግስቱ ስራ ስለሌላት ቁልፉን ሰጥቻት ሄድኩ፡፡ ምክንያቱም ቴሌቪዥን እንኳን እያየች ትዋል ብዬ ነው፡፡ ጊዜው ባዶ ቤት ውስጥ እንዴት ይሄድላታል? ምግብም አብስላ ብትበላ ትንሽ እቃ ስላለኝም ብዬ ነው፡፡ እኔው ቤት ዋለች ከስራ ስወጣ ምሳ የምትበላው ነገር እና ጫቴን ይዤ ሄድኩ፡፡ ቡና አፈላችልኝ…እኔው ጋር ዳግም አደረች፡፡ አሁን ግን አልተላለፍንም፡፡ በዛው ገባች በቃ!..ኪራዩ ቀረና ሌላ ሰው ተከራየው…ስራፈልጌ አስገባኋት፡፡

አልጋ ላይ ደስ የሚል ወሲብ ጣር አላት፡፡ በስሜ እየጠራች ‹‹ኡህ..ውይ..››በሚል ይጀመርና የእኔ ፍቅር፣ የእኔ ማር፣ የእኔ አንበሳ…ፍቅር ነህኮ ኡህ…ደስታን ካንተ አገኘሁ…›› ብዙ ብዙ ትላለች፡፡ ይህ ነገሯ ከለስላሳ ሙዚቃ የበለጠ ተመቸኝ፡፡ በጣምም ወደድኳት፡፡ ለሁለት አመት አብረን ኖርን፡፡ ጭፍን ያለ ፍቅር ውስጥ ገባሁ፡፡ ነገሩ የመጣው ከዚህ በኋላ ነው፡፡ ከምትሰራባቸው ሰዎች ሴት ልጅ ጋር ሲላመዱ ምስጢር ይገላለጡ ጀመር፡፡ የወንድ ጓደኛዋ ትውልደ ኢትዮጵያዊ እንደነበረ እና እንደተጣላት ነገረቻት፡፡ በባህላቸው ሴት ስታገባ ልጃገረድ ሆና ካልተገኘች ‹‹ጃንቢያ›› በሚባለው ሆዳቸው ላይ በሚታጠቁት ስለት እንዲገላት የሚፈቀድለት ወንድሟ ስለሆነ..እንዴት ጓደኛ ልትይዝ እንደቻለች የእኔዋ ልጅቷን ጠየቀቻት፡፡ በዛ ላይ ወንድና ሴት አንድ ላይ መሄድ አይቻልም እንዴት ትገናኛላችሁ? አለቻት፡፡

እናቷ በአደጋ ምክንያት አይናቸውን ሲታወሩ ትውልደ ኢትዮጵያዊው የሚፈልጉበት ቦታ እንዲያንቀሳቅሳቸው በሾፌርነት ተቀጠረ፡፡ ገብቶ ሲላመዱ እንደ ጀመሩ ነገረቻት፡፡ እናቷ አይኗን በመታወሯ ምክንያት አባትየው ስለፈታት ለብቻዋ ነው የምትኖረው፡፡ ልጅትም እሷ ጋር እሄዳለሁ ብላ ትሄዳለች፡፡ እሱ እዚያ በሾፌርነት ስለሚሰራ እዛው ይገናኛሉ..ሌላውንም ሌላውነም ብቻ ምስጢሯን ሁሉ አጫወተቻት፡፡ አያይዛም ሀበሻ ለፍቅር እንደሚሆን በትውልደ ሀበሻው እንዳየችና አንድ ሀበሻ እንድታስተዋውቃት ጠየቀቻት፡፡ ከመሳሳም ውጭ ምንም ማድረግ እንደማትፈልግ አሳወቀቻት፡፡ ወሮታውን 200 ዶላር ልትከፍል ለውንዱም የፈለገውን ልታደርግለት ስለተስማማች የእኔዋ ሚስት እድሉ ለሌላ እንዳይወጣ ፈልጋ አማከረችኝ፡፡ እኔም በጽዳት ሰርቼ የማገኛት ከሲጋራ፣ ጫት ሱሴ እና የቤት ኪራይ የማትዘል ሳንቲም ይልቅ በዚህ ጥሩ ልጠቀም እንደምችል ገምቼ ተስማማሁ፡፡..አለኝ ታሪኩን የሚያወጋኝ ወጣት፡፡

እዚህ ጋር የፍቅርን ህልውና እንድጠራጠር አደረገኝ፡፡ ሰው የሚወደውን ሰው እንዴት ለጥቅም ብሎ አሳልፎ ከሌላ ሰው ጋር እንዲሳሳም ያቀራርባል? የምወደውን ሰው እንኳን ለሌላ ማሳለፍ ቀርቶ ቅንጣት የጸጉሯን ስባሪ እንዲነኩብኝ አልፈልግም፡፡ ለነገሩ እዚህ አረቡ አለም ላይ ያሉ ጥቂት በጣም ጥቂት ኢትዮጵያዊያን ወንዶች ሴቷ ገላዋን ሸጣ የምታመጣውን ጠብቀው የሚኖሩ አሉ፡፡ እነዚህ ጥቅም ፈላጊዎች እንጂ ፍቅር ናፋቂዎች አይደሉም፡፡ ወይ ፍቅር…..

ከሱ ጋር ወዳወራሁት ስመለስ…. በስምምነታችን መሰረት የልጅቷ እናት ጋር በሳምንት ሶስት ቀን የጊቢውን አትክልት መንከከባከብ በሚል ሰበብ ተቀጠርኩ፡፡ ከልጅቷም ጋር እንደ ተባልኩት ተግባባን፡፡ ተጀመረ፡፡ ህሊናዬ ባይቀበለውም ከሚስቴ ጋር የማደርገው እያስመሰልኩ ህሊናዬ እየተሟገተ ገባሁበት፡፡ ከመሳሳም ያልዘለለ ግንኙነታችን ለትንሽ ጊዜ እንደተጓዘ መግባባት ስንጀምር በማይሆን ሁኔታ እንድንወስብ ጠየቀችኝ፡፡ ይህን አይነት ድርጊት እኔ ተጠቅሜ አላውቅም አንቺ ለምን በኋላ ማድጉን ፈለግሽ አልኩ፡፡ ስታገባ ድንግል ካልሆነች እንደሚገሉዋት እና በፊት ከነበረው ጓደኛዋ ጋር እንደዚህ እንደነበር የሚጠቀሙት ነገረችኝ፡፡

ከድርጊት በኋላ ተጋድመን ስታውራኝ ከእኔ ጋር ደስ የሚል ጊዜ ልታሳልፍ እንደፈለገችና የጠየቀችኝን እንቢ ማለቴ እንዳስከፋት ነገረችኝ፡፡ ስትቀጥልም..ሀበሻ ለፍቅር አመቺ እንደሆነ እሷ ብቻ ሳይሆን አባቷም ያውቃሉ፡፡ ሚስታቸውን የእሷን እናት መሆኑ ነው ከፈቱ ጀምሮ ከሰራተኛቸው ጋር እንደሚቀብጡ ታውቃለች፡፡ እንደተመቸቻቸውም ነግረዋታል፡፡ ልቤ ቀጥ አለ፡፡ የምሰማው ቅዠት እንጂ እውነት አልመስልህ አለኝ፡፡ ጆሮዬን የመስማት ጉጉት አርገበገበው፡፡ ለነገሩ በየቤቱ ሁለት ሶስት ሰራተኛ ሲለሚኖር ሌላዋን ይሆናል እንጂ የእኔዋን ውድ አይሆንም ሲል ውስጤ ውስጤን አጽናናው፡፡ ጠይቄ ቁርጡን ማውቅ ፈለኩኝ፡፡ ልቤ ግን ምቱን ጨምሮ ጉሮሮዬ ስር ተወተፈ፡፡ የሚገርም ነው በተፈጥሮዬ ለመጀመሪያ ጊዜ በመከዳት እንባ ተናነቀኝ፡፡ አላለቅሰው ምኔ ናት ልበላት? በምን አለቀስኩስ ብዬ ሰበብ ልስጥ? የእኔን በዝምታ ተለጉሜ መቆየት ሰብራ ወደ ወሬያችን እንድንመለስ ስትል ሳልጠይቃት ዘረገፈችው፡፡

ከሰራተኛቸው ፋጡማ ጋር ግንኙነት እንዳላቸው እና በጣም እንደተመቸቻቸው የነገሯትን አወራችኝ፡፡ ግንባሬ ላይ ችፍ ያለው ላብ ይሁን አይኔ፤ ላይ ታቁሮ የነበረው እንባ አላወኩም ጉንጬን ሰንጥቆ ወረደ፡፡ እልህ ተናነቀኝ፡፡ ግጥም አድርጌ መሳም ሳይሆን የመንከስ ያህል ትንፋሽ እስኪያጥራት ሳምኳት፡፡ በሁኔታዬ ግራ ተጋብታለች፡፡ ለፍቅሬ መታመን ስል ከመሳሳም ውጭ ሌላ ነገር ውስጥ እንዳልገባ ስታገል መቆየቴ አናደደኝ፡፡ ለፍቅሬ መታመን ስል ነበር ጠቀም ያለ ገንዘብ ልትሰጠኝ እናድርግ ያለችኝን እንቢ ያልኩት፡፡

ውስጤ ሌላ ሀሳብ አፈለቀ፡፡ ያለችኝን እንቢ ስለላኩዋት ሌላው ሀበሻ ያደርጋል ብላ ለማሳመን ውሸቷን ቢሆንስ? ደግሞ አባትስ ከእናቷ ውጭ ሌላ ሴት ማድረጋቸውን እንዴት ሊነግሩዋት ቻሉ? ውሸቷን ነው የሚል ሀሳብ ነበር፡፡ ምነው እንዳሰብኩት ውሸት በሆነና እፎይ ባልኩ፡፡ ያሰብኩትን ሀሳብ አቀረብኩላት፡፡ ምን አቀጣቅጧት እቴ…ምን ታድርግ ቁስሌ አልገባት..የፍቅሬ መናድ አያሳዝናት….ለምኗ ብላ ትሸሽገው? እንኳን እኔ አንዱ ደካማ ሰው ይቅርና ወገኔ ያልኩት ሁሉ የማይችለውን ጉድ ዘረገፈችልኝ፡፡ ከሀያ ቀን በፊት እሷ ራሷ በዚህ ተግባር ላይ እያሉ ይዛቸው ስትቆጣ አባቷ ከእናቷ ፍቺ በኋላ ፋጡማ ስለተስማማቻቸው እንደሆን ቶሎ ማግባት ያልፈለጉት እንደነገሯት ጭምር ስትነግረኝ የምይዝ የምጨብጠውን አጣሁ፡፡ እሷ ግን ቀጠለች፡፡ እንዳይወልድ መጠንቀቅ እንዳለበት ለስሙ ጥሩ አንዳልሆነ ስነግረው ‹‹..ከዚህ በኋላ እጠነቀቃለሁ፡፡ ባለፈው አርግዛ እንድታስወርድ አደረኩኝ..›› አለኝ፡፡ እሱ ወንድ ስለሆነ ነው የሚናገረው እኔ ብሆን ግን ይገሉኛል ለዚህ ነው…እያለች ታወራልች፡፡ እኔ ግን አስብ የነበረው ሳንደራጅ፣ ተቀማጭ ሳይኖረን፣ በዚህ ኑሮ መውለድ የለብንም ብላ አሳምናኝ ያደረገችው ውርጃ የአባቷ ጽንስ ቢወለድ ኖሮ የሚከሰተውን ነው፡፡

ክዳቷ ውስጤን በቁጭት አርመጠመጠው፡፡ የጠየቀችኝን ተቀብዬ ስንተኛ ወዴ ፍቅሬ በ200 ዶላር አሳልፍ እንደሸጠችኝ እያሰብኩ ነበር፡፡ በእልህ የጀመርኩት ነገር ግን ባላሰብኩት ሁኔታ ቀጠለ፡፡ ከኋላ ትቼ በተፈራው ቦታ ገባሁበት፡፡ ከዚህ በኋላ ህይወቴ አደጋ ላይ እንደሆነ አውቃልሁ ያወቁ ቀን ይገሉኛል፡፡ ያለኝ አማራጭ ወደ ሳዑዲያ መጥፋት ብቻ ነው፡፡ ሀገሬ የምገባበት ፓስፖርት የለኝ፡፡….አይኖቹ እንባ አቅርረው ስለነበር ጥያቄ ቢኖረኝም የባሰ ሆድ ማስባስ ስለሆነብኝ ተውኩት፡፡ እሱ ግን ‹‹..እሷ እኔ አለሁ አይነኩህም ብላ እንደሰጠችኝ ተስፋ በተስፋ ተሰንጌ መኖር አለበለዚያ በተለያየ መንገድ ከዚህ የምውጣበትን መፈለግ ካልሆነም ሞት መጠበቅ ነው እጣዬ…ይሄው ነው ከፈለክ ጻፈው፡፡ ካፈለክ…›› ብሎኝ ሊሄድ ተነሳ፡፡ ሚስትህስ አሁን በምን ሁኔታ ናት? መለስ ብሎ ስልኬን ከእጄ ወሰደ እና ቁጥሯን ጽፎ ‹‹..ያን ዜና ከሰማሁበት ቀን ጀምሮ አላየኋትም፡፡ ከፈለክ ደውልና ጠይቃት፡፡ ላንተም ይደርስህ ይሆናል..›› ብሎኝ ወጣ፡፡ ስርዓት ያጣው አነጋገሩ ቢያናድደኝም ምላሽ አልሰጠሁትም፡፡ ሆድ የባሰው በመሆኑ የሚናገረውን አያውቅም ወይ ስሜታዊ ሆኖ ነው ብዬ አለፍኩት፡፡

ባለፈው ልጇ እና ባሏ ላይ የፈላ ዘይት የደፋችው ሴት በፍርድ ቤት የተፈረደባትን ፍርድ በቀጣዩ አሳውቃለሁ ብዬ ነበር፡፡ ፍርዱ ሞት ነው፡፡ ግን ፍርዱ የሚፈጸመው ህጻኑ ባለበት መሆን ስላለበት ልጁ 18 አመት እስኪሞላው እስር ቤት እንድትቆይ ተውሰኗል፡፡
በቀጠይ ዘና በሚያደርግ ጽሁፍ እንገናኛለን፡፡
ቸር ይግጠመን፡፡

ጥቁሯ ቦርሳዬ ክፍል 7
‹‹…ለአራጅነቱ ሪፈር ወደ ቄራ ››
ወግ በግሩም ተ/ሀይማኖት

ስላም ጤና ፍቅር ለእናንተ ይሁን! አሜን አትሉም፡፡ የእዚህ ክፍል ንዑስ መልዕክት ወይም ጥቅስ..‹‹በፍቅር፣ በመረዳዳት፣ በመተሳሰብ፣ በመከባበር፣ በጋር ለመኖር በግልጽ እንነጋገር እንወያይ..›› የሚል ነው፡፡ ፍቅር እንዲያስተሳስረን በግልጽ መወያየት ግድ ይላል፡፡ በፍቅር የመኖርን ያህል ምን ነገር ያስደስታል? ታዲያ በፍቅር ስም ከሚነግዱ ስሙን ታዛ ከለላ አድርገው ከሚሸቅጡ አጭርባሪዎች፣ የፍቅር ሸቃጮች ራሳችሁን ጠብቁ…በየዋህነት በፍቅር ስም ራሳችሁን አትገብሩ፡፡ በየዋህነት በአስትሮሎጂ ምክንያት እንደጠፋው ድንግል እንዳትሆኑ….ኪኪኪኪ… ሳስበው ያ-ትዝታ ያስቀኛል፡፡ በእናንተ አትሮሎጂ ድንግሌን አጣሁ ብላ የመጣችው ልጅ ታሪክ ዛሬም ድረስ ስለ የዋሆች ሳስብ ጣፋጭ ትዝታዬ ነው፡፡

ራህዋ የምትባል ልጅ ናት አንድ የጋዜጣ ዝግጅት ክፍል ቢሮ ውስጥ በእንግድነት ጓደኛዬ ጋር ቁጭ ብዬ መጣች፡፡ ‹‹..በእናንተ አስትሮሎጂ ጉድ ሆንኩ ድንግሌን አጣሁ..›› ስትል ጥርሴ መጣብኝና ሳኩኝ፡፡ ሳቄ ሳያሸማቅቃት ቀጠለች፡፡ እዛ ዝግጅት ክፍል ስራተኛ ባልሆንም በእንግድነት ቁጭ ብዬ ይሄን ገጠመኝ ላጋጠመኝ አምላክ ምስጋና አቅርቤ ለመስማት የጆሮዬን ፍሪኩዌንሲ አስተካከልኩ፡፡ የሰማሁትን ሪከርድ ማድረጊያ ቅንጭላቴን ከፍቼ…ምን አለፋችሁ ብቻ ሬዲ የሚለው ላይ ክሊክ አደረኩና….ጀመረች፡፡ እኔም በራሴ አጻጻፍ ጀመርኩት…….

ልጅት ቀጠለች…ማን እንዳይሉኝ ስለ ራህዋ ነው የማወራው፡፡ አስትሮሎጂ አፍቃሪ ናት፡፡ አስትሮሎጂ አሳዳጅ ናት፡፡ የሚለው ሁሉ እውነት ይመስላታል፡፡ የአስትሮኖመሮች ግምት እና ቀመሩ በስሌት የሚመጣ መሆኑን ማን በነገራት፡፡ እኛ ሀገር ደግሞ አስትሮኖመሮች የጻፉትን መተርጎም ብቻ ሳይሆን ጫቶኖመሮችም ይጽፉታል፡፡ እነዚህ ደግሞ ምንድን ናቸው ካላችሁ ጫት ላይ ቁጭ ብለው ደስ ያላቸውን ገምተው የሚጽፉ ናቸው፡፡ የሚገርመው ገጠመልን፣ ሆነልን የሚሉ ሰዎች መኖራቸው ነው፡፡ የጋዜጣውን ርዕስ የማልጠቅሰው ጋዜጣችንን አብጠለጠለ ብለው የኩርፊያ በትራቸውን እንደ ስኩድ ሚሳይል በስደት ያለሁበት ሀገር ድረስ እንዳያስወነጭፉብኝ ነው፡፡ እዚህ ጋር በፍቅር እንኑር እያልኩ ኩርፊያ ራሴ ላይ ማምጣት የለብኝም፡፡ ኩርፊያ ፍቅርን የሚያጠፋ ረመጥ ነው የሚል አቋም አለኝ፡፡ ስለዚህ ራሴ ላይ ኩርፊያ አልጋብዝም፡፡ ጋዜጣው ግን ሞቶ ነፍስ ይማር እየተባለ በነበር ሲጠራ ከርሟል፡፡ አሁን ግን አልጠራውም፡፡ ነፍስ ይማርም አልልም ዳግም ምጽዓቱን ያቅርብለት እንጂ..፡፡

ስለ አስትሮሎጂ ሳወራ ትዝ የሚለኝ ብዙ ነገር አለ፡፡ ከሞያ ጓደኞቼ ውስጥ ደግሞ በተለያየ ገጠመኝ ሰለሞን ሙሉ ታፈስ እና ከበደ ደበሌ ሮቢ ትዝ አሉኝ፡፡ የት ይሆን ያላችሁት? ራህዋ እና አስትሮሎጂ ቁርኝታቸው መቼ እንደሚጀምር አላውቅም፡፡ ብቻ ጋዜጣ ስታገኝ ቶሎ፣ ገልብጣ ሊብራ የሚለው ስር የሰፈረውን ታያለች፡፡ ጥሩ ከሆነ ፈግጋ ሳቅ ሳቅ ሲላት፣ መጥፎ ከሆነ ደምና በኩርፊያ ተጠፍንጋ…ትውላለች፡፡ በቃ! የራህዋ የባህሪ እና የፊቷ ሁኔታ እንደ አየር ሁኔታ በሚትሪዎሎጂ ሳይሆን በአስትሮሎጂ የሚወሰን ነው፡፡

አንድ ቅዳሜ ጠዋት ፈገግ ኮስትር የሚያደርግ ነገር ገጠማት፡፡ እሷ ኮኮብ ስር ‹‹..የፍቅር ሰው የሆኑት ሊብራዎች በእዚህ ሳምንት የፍቅር ህይወታቸው ላይ የሚጋረጥ መሰናክል አለ፡፡ ብልጥ ከሆኑ የሚያልፉበት መንገድም አለ፡፡ ከፍቅረኛዎ የሚቀርብልዎትን ሀሳብ በእሺታ ያሳልፉት እቃወማለሁ ቢሉ የፍቅር ህይወትዎን ያበላሻሉ…›› ጭንቅ ጥብ ነገር ተፈጠረ፡፡ የሀሳብ ጥንግ ድርብ እሷ ላይ ሰፈረ፡፡ ፍቅረኛዋ ሁሌም እየጠየቃት የሚጣሉት ህብረ አንሶላ እንፍጠር ነው፤ ሴትነትሽን ልፈትሸው ነው፡፡ በሌላ አባባል ከልጃገረድነት ወደ ሙሉ ሴትነት ልለውጥሽ እያላት ነው፡፡ በአራዳ ልጆች አባባል እንደ ልብሽ እንድትሸኚ ላርግሽ እያላት ነው፡፡ ቆይ ግን ያልገባኝ ይሄ ነገር እንደልብ አያሸናም እንዴ? እውነት ከሆነ የሆኑት ተጨንቀዋላ?...

እሷ ደግሞ ጠብቃ ያቆየችውን ክብር መጠበቅ ነው ፍላጎቷ፡፡ ለባህልና ቅርስ ተንከባካቢ ኮሚቴ ትስጠው፣ ለአዋሽ ቆዳ ፋብሪካ ታውርሰው፣ ለጋብቻዋ ገፀ- በረከት ታድርገው ሁሉም የራሷ ምርጫ ነው፡፡

አልሰጥም አትል ነገር ፍቅረኛዋን መለየት አትፈልግም፡፡ ትወደዋለች፡፡ እሱን ከምታጣ ‹‹…ክብሬን ሳትል ማዕረጌን አቤት ብቻ ነው ሲጣሩ እቴጌ…››የሚለውን ማቀንቀን ትመርጣለች፡፡ አጋጣሚ ነገር ሆነና እሱም ከዩነቨርስቲ ትምህርቱ እሷም ከስራዋ እረፍት የሚሆኑበት እና ዘውትር አብረው የሚያሳልፉት እሁድ ላይ ጠየቃት፡፡ እንዴት እንቢ ትበል? ታወሳት አስትሮሎጂው፡፡ ገጥሞላት የማያውቀው አስትሮሎጂ ገጥሞባት እጅ ሰጠች፡፡ ምን እጅ ብቻ እግርም ሰጠች፡፡ ሆነ….ጫጉላው አብቧል አልተባለ፣ ብራምባር ሰበረልሽ የለ…የቤርጎ አንሶላ አቅልተው የሳሙና ከፍለው ወጡ፡፡

በቀጣዩ ቅዳሜ እዛው ጋዜጣ ላይ ‹‹..ሰሞኑን በሚገጥሞት ነገር አይደናገጡ፡፡ ባለፈው ሳምንት በሰሩት ነገርም አይፀፀቱ በዚህ ሳምንት ከፍቅረኛዎ ደስ የማይል ዜና ይሰማሉ…›› እያለ ይወርዳል፡፡አልቀረም እሁድ እሁድ የሚገናኙበት ቦታ የለም፡፡ ጭንቅ ጥብ ሆነ፣ ተስፋ መቁረጥ የተከመረበት ፍርሃት ነገሰባት፡፡ ፍለጋው አያልቅም የሚለውን እያዜመች ፍለጋዋን ቀጠለች፡፡ ተገኘ ልጁ ተገኘ የሚለውን ለልቧ አዚማ ‹‹..ምነው? ሆዴ ባልተለመደ ሁኔታ…›› ብትል እንደማይፈልጋት ነገሯት ቁጭ፡፡ እሷ ስትናገር ምነው ስለው….ነው ያለችው ባልተለመደ ሁኔታ የሚለውን በሀሳብ ስስላት የጨመርኩት ነው፡፡ ጠብቃ ያቆየችውን በአስትሮሎጂ ተማርካ አስረከበች፡፡ ከእንዲህ አይነት ገጠመኝ ይሰውራችሁ…..፡፡

የየዋሆቹን ትቼ ወደ የመን ሀበሾች ስመለስ ባለፈው ካሰፈርኩት ታሪክ ስር ቅድስት ተክሌ የተባለች ልጅ ‹‹..ለሁላችንም የልብ ድንግልና ይስጠን::…›› ብላለች፡፡ በትልቁ አሜን ከተገኘስ የልብ ድንግልና ይሰጠኝ ብያለሁ፡፡ እናንተም ለራሳችሁ አሜን በሉ፡፡ ሁለት ይሁኑ ሶስት ሰዎች የጭን ድንግልና ከሌለ እንዴት የልብ ድንግልና ይኖራል፣ የጭን ድንግልና ይበልጣል ያሉ አሉ፡፡ ሁሉም በራሱ አመለካከት ልክ ነው፡፡ ግን አስተውሎ መራመድን የመሰለ ነገር የለም፡፡ ከልብ ይልቅ የጭን ድንግልና የመረጠውን ደም ለማፍሰስ አምሮቱ፣ ለአራጅነቱ ሪፈር ወደ ቄራ ቢላክ ያዋጣዋል፡፡ ሄለን የተባለች የመን ያለች ስደተኛ ‹‹..ባሏን ስለገደለችው ሴት ለምን አትጽፍም ብላኝ ነበር፡፡ ይህን ታሪክ ዜና ሰርቼው ነበር፡፡ ልመለስበት ወደድኩ፡፡

የመን በተለይ ሰነዓ ጆሮ እንስጥ እንጂ የማይሰማ የለም፡፡ እንኳን ሰዉ ንፋሱ ወሬ ያመጣል፡፡ አሁን የምናገረው እውነተኛ ታሪክ መሆኑን ልብ በሉ፡፡ ታዲያ ሚስቶቻችን ቀን ቀን የአረብ ማታ ማታ የእኛ የሚለውን የአንዳንድ ባሎች አባባል አስታውሱልኝ፡፡ አሚናት ትባላለች ኢትዮጵያዊት ናት፡፡ ቆንጆ ባትሆንም አስጠሊታ አይደለችም፡፡ አስጠሊታው ውስጣችን እንዳይሆን እንጂ ውጫችን እንዳይሆን መጠንቀቅ የለብንም፡፡ ውበት ከውስጥ ነው፡፡

ከያሲን ጋር አብረው መኖር ከጀመሩ አምስት ዝርክርክ አመታትን አሳልፈዋል፡፡ በጭቅጭቅ፣ በቅናት..በኩርፊያ የታጀቡ 5 አመታት፡፡ ተነጋግሮ መረዳዳት፣ መተማመን ባለመቻላቸው የቅናት ዛር አዶከብሬውን ይዞ ጎጇቸው ላይ ይጨፍር ጀመር፡፡ ቅናት እንዲያጠፋ ይሁን ቅናት እንዲያፋፍም ልጅ ወለዱ፡፡ ባልተረጋጋ የትዳር ህይወት ላይ ያሉ ሰዎች መውለድን ባያስቡት እንዴት ደስ ይላል? ወልደው ለእነሱ ያልጣመቸውን ህይወት በቆርፋዳ መልኩ ሊያጋፍጡት መውለድ ብልግና ነው፡፡ ከእደዚህ አይነት ቤተሰብ ተወልደው ለጭንቅ ጥብ የተዳረጉ ስንት ዜጎቻችን ይሆኑ?

ገባ ወጣ../ሌላ ነገር አላልኩም/ አመሸህ፣የት ነበርክ?…አቤት ቅናት ያበቀለ ትዳር እንኳን ልጅ ሊወለድበት ጎረቤትም አይኖርበት፡፡ አሚናት የፈሲታ ተቆጢታ እንደሚሉት አይነት ባሏ በወጣ በገባ ቁጥር ትነዘንዘው ጀመረች፡፡

ከዕለታት አንዱ በተረገመ ፍጻሜ እለት አገር አማን ብሎ ልጁን ታቅፎ የተኛ ባለቤቷን እና የዘጠኝ ወር ህፃን ልጇን ቁርስ ትሰራላቸዋለች፡፡ የሚበሉት ቁርስ ሳይሆን ሞትን የሚያጣጥሙበት ቁርስ፡፡ ዘይት አፍልታ ደፋችባቸው፡፡ ተሰውራ ከረመች፡፡ ልጇም ሆነ ባሏ ያሲን በህክምና ቢረዱም ባሏ ከፍተኛ አደጋ የደረሰበት በመሆኑ አልተረፈም፡፡ ያሲን ጁሜሪ የሚባለው ሆስፒታል ገብቶ ለሁለት ቀን እርዳታ ቢደረግለትም ራስ ቅሉ ላይ በደረሰው ከፍተኛ አደጋ ምክንያት ሊተርፍ አልቻለም፣ ሞተ፡፡ ትንሽ ልጃቸው አሁን ከፍተኛ ህክምና ተደርጎለት በአንድ በጎ ምስኪን ሴት እናትነት እያደገ ነው፡፡ ፊቱን ራስ ቅሉ ብሎም ጀርባው ላይ ከፍተኛ ጉዳት የደረሰበት ህጻን ገና ከፍተኛ ቀዶ ጥገና ያስፈልገዋል እየተባለ ነው፡፡ ደብዛዛ ቢሆንም ከላይ ያለውን ፎቶ ይመልከቱ፡፡ በወቅቱ ፊቱ በመጎዳቱ ምክንያት ፕላስቲክ ሰርጅሪ መደረግ እንዳለበት የህክምና ባለሞያው ገልፀው በዛው ቀረ፡፡ ዛሬ ግን ከፍተኛ ህክምና ማግኘት ቀርቶ ለነፍስ ያሉ አሳዳጊው የሚበላውንም እየተቸገሩ ነው የሚያሳድጎት፡፡

ይህን አሰቃቂ ሁኔታ ፈጽማ የተሰወረችው አሚናት ከወር በኋላ ተያዘች፡፡ ዘይት አፍልታ የደፋችበትን ምክንያት ስትናገር ‹‹አናዶኝ ነው እኔ ተቃጠልኩ አልቻልኩም፡፡ ሌላ ሴት ጋር እየሄደ አስቸገረኝ፡፡ አልፎ ተርፎ እጅ ከፍንጅ ያዝኩት..ይህን ድርጊት የፈጸምኩት ተናድጄ ነው..››አለች፡፡ ይሄኛው አዲስ ግኝት ሳይሆን አይቀርም ለንዴት ማብረጃ ዘይት አፍልቶ…ሆሆይይይ…የጉራጌ ብስኩት አደረገችው እንዴ በዘይት የምትጠብሰው? ደግሞ እኮ ሰነዓ የሰው ሚስት ይዞ፣ የሰው ባል ይዞ ተኝቶ መገኘት አዲስ እና የሚያሳፍር አይደለም፡፡ አንዳንድ ገገማ ደግሞ አለላችሁ ፍጥጥ… ምንም አላረግንም፡፡ አስቡ እስኪ ልብስ አውልቀው በር ዘግተው እየተያዙ ምንም አላረግንም…ታዲያ ለፀሎት ነው በር የዘጉት? በር መዝጋቱ ለጸሎት ይሁን ልብስ ማውለቁስ? ለምንድን ነው ለምርመራ!. ኪኪኪከኪ…

ትልቁ ችግር እኛ ንጹህ ነን ወይ የሚለውን ሳይሆን ሁሉም የሰው ነው የሚያብጠለጥለው፡፡ አሚናትም ይህን አስባ ራሷን ብትፈትሽ ለዚህ አይነት ጭካኔ ባልተዳረገች፡፡ እሷስ ለትዳሯ ታማኝ ነች ወይ? ብለን ብናስብ ሊከብድ ይችላል፡፡
ይህን ቃል አጥብቀን እንደያዝን ወደ ታሪካችን እንመለስ፡፡ የሚያሳዝነው እና አሳዛኙ ድርጊት የተፈጸመው ያለ ምክንያት መሆኑ ነው፡፡ ያሲን እሷ ያለችውን አላረገም ማለቴ አይደለም፡፡ ማድረጉንም አላውቅም፡፡ ግን አደጋውን አድርሳ ለአንድ ወር ያህል ራሷን ደብቃ ከረመች፡፡ ጠፍታ የተሰወረችበት ቦታ ድረስ መርቶ ያሲያዛት ከበፊት ጀምሮ በውሽምነት ይዛው የነበረ የመናዊ መሆኑ ነው ደግሞ ዝንጀሮ የራሷን መቀመጫ ሳታይ የሚያስብለው፡፡ ለዚህም ነው ያለ ምክንያት ያልኩት፡፡ ራሷ እየተሰረቀች እሱ አደረገ ብሎ መንጨርጨር….

አዲስ ሲም ካርድ ገዝታ ከመናዊው የባል ተደራቢ ጋር ብቻ ለመገናኘት አስባ ትደውልለታለች፡፡ በድርጊቷ ተናዶ ስለነበር የት እንዳለች ጠይቆ ሲያበቃ እንዲገናኙ እንደምትፈልግ ስትነግረው ቀጠራት፡፡ ቦታው ድረስ ፖሊስ ይዞ በመሄድ አስያዛት፡፡ በባሏ ላይ የሸረሞጠች ሴት በውሽሟ ላይ..እንደሚባለው ባሏን የገደለች ነግ ለእሱም የማትመለስ መሆኑን በየመኒኛ አስልቶት ይሆን ያስያዛት? ወይስ በስርቆት የሰራውን ሀጢያት በዚህ አካክሶ እንደ ጲላጦስ ከደሙ ንጹህ ነኝ ሊል ?

ሰው አብሮ የበላው፣ አብሮ የጠጣውን ትዳሬ አካሌ፣ አምሳሌ ያለው ላይ ይህን መሳይ አሰቃቂ ድርጊት ለመፈጸም እንዴት ይነሳል? ያውም እሷ ያልጠበቀቸውን እምነት አጎደለ ብሎ…ሰማንያ ሲያደርጉ እሱ በአክሲዮን ግዢ መልክ /ወይም ጨረታ/ ሊጠቀም እሷ በሞኖፖል ልትጠቀልለው ነው የተስማሙት?

እሺ ባሏ አጥፍቶ ሊሆንም ላይሆንም ቢችል እንኳን የዘጠኝ ወር ህፃን አብሮ እንዲቃጠል የተደረገበት ምክንያት ምንድን ነው? አልተገለፀም፡፡ መጨካከን ካልሆነ እናት የፈለገ ብትናደድ ለልጇ ብላ አትተውም? <<..ጎሽ ለልጇ ስትል…›› ብለው የተረቱት እናቶች ይህን እንዴት ይሰሙት ይሆን? ወይስ ‹‹ጎሽ ለባሏ ብላ ልጇን ቀቀለች..›› ብለው ይቀይሩታል፡፡

ፍ/ቤት የወሰነባትን በሚቀጥለው አስነብባለሁ፡፡ እርሶ ቢሆኑ ምን ይፈርዱባት ነበር?
አንድ ጣትህን ወደ ሰው ስትቀስር ሶስቱ የታጠፉት ወደ አንተ ማመልከታቸውን አትርሳ የሚለውን አስበን እንሰነባበት፡፡
በፍቅር እንሰንብት